ጥራት ያለው ትምህርት ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ መንግስት ከሚያደርገው ጥረት በተጨማሪ የባለሀብቱ ተሳትፎና ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በጉራጌ ዞን የእኖር ኤነር ወረዳ ትምህርት ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡

በባለሀብቱ በአቶ ወርቁ ሽራጋ የተገነባው የአንዘቸ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ ተጠናቆ ለመማር ማስተማር ስራ ዝግጁ መሆኑንም ተጠቁሟል፡፡

የትምህርት ቤቱ ግንባታ አስመልክቶ ባለሀብቱ አቶ ወርቁ ሽራጋ እንደገለጹት ኢህዓዴግ ሀገሪቱን ሲቆጣጠር ከዚህ ቀደም የነበረውን የትምህርት ፖሊሲ በመቀየሩ የአንዘቸ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመማሪያ ክፍል እጥረት ምክንያት ከ1ኛ እስከ 6ኛ ክፍል ከሚያስተምርበት ዝቅ ብሎ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ብቻ እንዲያስተምር ተወስኖ እንደነበር ያስታወሱት እኚህ ባለሀብት ተጨማሪ ግንባታ በማካሄድ በወቅቱ የነብረውን የመማሪ ክፍል ችግር ተቀርፎ ትምህርት ቤቱ ደረጃውን ሳይቀንስ እስከ 8ኛ ክፍል እንዲያድግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸዉም ተናግረዋል፡፡

ከ1993 ዓመተ ምህረት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ለትምህርት ቤቱ የሚያስፈልጉ ግንባታዎች ብቻውን በመገንባት ትምህርት ቤቱ እስከ 12ኛ ክፍል በማሳደግ ለአካባቢው ማህበረሰብ ያለምንም እንግልት ልጆቹን በቅርበት እያስተማረ ሀገራቸውን የሚጠቅሙ ትውልድ ለማፍራት አጋዥ እንደሆነም አመላክተዋል።

አክለውም በትምህርት ቤቱ ግቢ ውስጥ የነበረ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት በማፍረስ ለህጻናት ምቹ በሆነ መልኩ ደረጃውን የጠበቀ ግንባታ ገንብተው ለትምህርት ቤቱ ያስረከቡ ሲሆን ለትምህርት ቤቱ የሚያስፈልጉ ግብዓት የማሟላት ስራ መስራታቸውን ተናግረዋል፡፡

መምህራኖች ተረጋግተው የመማር ማስተማር ስራው በጥራት እንዲያከናውኑ ደረጃቸውን የጠበቁ 34 መኖሪያ ቤቶች ገንብቶ ያስረከቡ ሲሆን በቀጣይም ተጨማሪ 17 ቤቶችንም እንደሚገነቡ የገለጹት እኚህ ባለሀብት እስካሁን ለትምህርት ቤቱ ግንባታ ከ30 ሚሊዮን ብር ባላይ ወጪ ማድረጋቸውንም ተናግረዋል፡፡

በርክክቡ ወቅት የተገኙት የእኖር ኤነር ወረዳ የትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ማሩፍ አብድሽኩር በበኩላቸው ጥራት ያለው ትምህርት ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ ወጪ በማድረግ በትምህርት ላይ እያደረጉት ያለውን ኢንቨስትመንት ከትውልድ ትውልድ የሚሸጋገርና የመንግስትንም ክፍተት የሚሞላ አርዓያነት ያለው ተግባር ነዉ ብለዋል፡፡

ከ1ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ በማስተማር ላይ የሚገኘውን የአንዘቸ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ተማሪዎች ምቹና ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት መማር እንዲችሉ አጠቃላይ ግንባታ ብቻቸውን በመገንባት የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ማድረግ በመቻላቸው ኃላፊው ላቅ ያለ ምስጋና አቅርበዋል፡።

ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ መስፍን ክነፈ በሰጡት አስተያየት ከዚህ ቀደም ልጆች እስከ ስምንተኛ ክፍል ከተማሩ በኋላ ስንቅ ቋጥረው ወደ ሩቅ ቦታ ሄደው መማር ስለማይችሉ አቋርጠው ወደ አዲስ አበባና ወደ ሌላ አካባቢዎች በመሄድ በተለያዩ አነስተኛ ስራ ይሰማሩ እንደነበር አስታውሰው አቶ ወርቁ ሽራጋ ይህንን ት/ቤት በመገንባታቸው ተማሪዎች ሳያቋርጡ ትምህርታቸውን በቅርበት እንዲማሩ አስችሏል ብለዋል፡፡

አክለውም ከትምህርት ቤቱ ተምረው ጥሩ ውጤት በማምጣት በተለያየ ደረጀ ላይ ሆነው ሀገራቸውን በማገልገል ላይ ይገኛሉ ያሉት አቶ መስፍን ህብረተሰቡም ትምህርት ቤቱ አስፈላጊውን እንክብካቤ እያደረገለት እንደ አይን ብሌኑ ይጠብቀዋል ብለዋል፡፡

በትምርት ቤቱ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ አግኝተን ካነጋገርናቸው ተማሪዎች መካከል ሰሚራ አወል፣ መልካም ወ/ጻዲቅ እና አብድልሃሚድ ኑሩ ይገኙበታል፡፡ ሁሉም በሰጡት አስተያየት ትምህርታቸውን ጠንክረው በመማር ጥሩ ውጤት አምጥተው ሀገራቸውን በታማኝነት በማገልገል የባለሃብቱ የአቶ ወርቁ ሽራጋ ውለታ እንደሚመልሱ ተናግረዋል ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ነው።

  • አካባቢህን ጠብቅ !
  • ወደ ግንባር ዝመት !
  • መከላከያን ደግፍ!

በተጨማሪም እነዚህ ሊንኮችን በመጫን ወቅታዊና ትኩስ መረጃዎቻችንን እንድትከታተሉ እንጋብዛለን፡፡
Facebook:- https://www.facebook.com/gurage1Zone
Website:- https://gurage.gov.et
Telegram:- https://t.me/comminuca
Youtub: -https://www.youtube.com/channel/UCzrcazGvvIO2tG7bQN36Cx

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *