ስፖርት የወጣቶች ስብዕና ከመገንባት በተጨማሪ የማህበረሰቡ የወንድማማችነት እሴት ለማጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት የጉራጌ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ገለፀ።

የጉራጌ ዞን የ2014 የልዩ ልዩ ስፖርታዊ ሻምፒዮና እና የባህል ስፖርት ውድድር በቡታጅራ ከተማ ተጀምሯል።

የጉራጌ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አወል ጅማቶ የዞኑ ስፖርታዊ ሻምፒዮና ባስጀመሩበት ወቅት እንደተናገሩት የዘንድሮ ውድድር በዞኑ በመስቃንና ማረቆ ወረዳ ወንድማማቾች መካከል የነበረው ግጭት በእርቅ በተፈታበት ማግስት መካሄዱ ልዩ ያደርገዋል።

ስፖርት የዜጎች አእምሯዊ፣ አካላዊ፣ ስነልቦናዊ ብቃት ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት የተናገሩት አቶ አወል የዞኑ ህዝብ ያሉትን የወንድማማችነት እሴት በማጠናከር የህብረተሰቡን ግንኙነት እንዲጎለብት ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው ብለዋል።

ስፖርት ከመለያየት ይልቅ የመቀራረብ፣ከመጣላት ይልቅ የመፈቃቀር ኃይል ያለው በመሆኑ በዞኑ የሚስተዋለው ሰላም ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ ሁሉም በንቃት መሳተፍ እንደሚጠበቅበት አስረድተዋል።

በቀጣይ ቀናት የሚካሄዱ ሁሉም የውድድር መድረኮች በፍጹም ስፖርታዊ ጨዋነት እንዲጠናቀቁ ማድረግ ይገባል ያሉት አቶ አወል ዞኑን የሚወክሉ ተተኪ ስፖርተኞች የሚመለመሉበት መድረክ በመሆኑ ተወዳዳሪዎች ስፖርታዊ ጨዋነት ተላብሰው መጫወት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

የቡታጅራ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ሺፋ መሀመድ በበኩላቸው ዞናዊ ውድድሩ በስኬት እንዲጠናቀቅ የቅድመ ዝግጅት ስራ የተሰራ ሲሆን ሶስት እስቴዲየሞች ለውድድር ዝግጁ ተደርገዋል ብለዋል።

ተወዳዳሪዎችና ሌሎች የስፖርት ልዑካን ቡድን በከተማው በሚኖራቸው ቆይታ ደስተኛ እንዲሆኑ፣ደህንነታቸው የተጠበቀ፣ ምቹና ደረጃቸውን የጠበቁ ማረፊያዎች ከማመቻቸት በተጨማሪ የከተማው ሰላም ለማስጠበቅ ከጸጥታ ኃይሎች ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል።

በመምሪያው የስፖርት ዘርፍ ኃላፊ አቶ አደም ሽኩር የጉራጌ ዞን የ2014 ልዩ ልዩ ስፖርታዊ ሻምፒዮና እና የባህል ስፖርት ውድድር በዘጠኝ የስፖርት ዘርፎች ይካሄዳል ብለዋል።

እነዚህም እግርኳስ፣ አትሌቲክስ፣ ቮሊቦል ፣ ፓራሎምፒክስ፣ ቴኳንዶ፣ ብስክሌት እና የተለያዩ የባህል ስፖርቶች እንደሆኑ አቶ አደም ገልጸዋል።

ውድድሩ የማህበረሰብ ትስስር ከማጠናከር ባሻገር በተለያዩ የስፖርት አይነቶች ዞኑን የሚወክሉ ተተኪ ስፖርተኞች ለማፍራት ያግዛል ብለዋል አቶ አደም ።

የውድድሩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ከተማው ያደረገላቸው አቀባበልና ለውድድሩ የተደረገው ዝግጅት አስደሳች ነው ብለዋል።

ውድድሩ እስኪጠናቀቅ ስፖርታዊ ጨዋነት ተላብሰው ቡድኖቻቸው ውጤታማ እንዲሆኑ እንሰራለን ሲሉም ገልፀዋል።

= ኢትዮጵያን እናልማ!
= የፈረሰውን እንገንባ!
= ለፈተና እንዘጋጅ!

በተጨማሪም እነዚህ ሊንኮችን በመጫን ወቅታዊና ትኩስ መረጃዎቻችንን እንድትከታተሉ እንጋብዛለን፡፡

Facebook:- https://www.facebook.com/gurage1Zone
Website:- https://gurage.gov.et
Telegram:- https://t.me/comminuca
Youtub: -https://www.youtube.com/channel/UCzrcazGvvIO2tG7bQN36Cx

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *